5ኛው አዲስ ቻምበር ዓለም አቀፍ የማኑፋክቸሪንግና የቴክኖሎጂ ንግድ ትርዒት በአዲስ አበባ ተከፈተ

አዲስ አበበ ህዳር 8/2015 (ኢዜአ) 5ኛው አዲስ ቻምበር ዓለም አቀፍ የማኑፋክቸሪንግና የቴክኖሎጂ ንግድ ትርዒት ዛሬ በአዲስ አበባ ኤግዚቢሽን ማዕከል ተከፍቷል፡፡ በመክፈቻ መርሃ ግብሩ ላይ የኢንዱስትሪ ሚኒስትር መላኩ አለበል፣ የአዲስ አበባ ንግድና ዘርፍ ማህበራት ምክር ቤት ፕሬዚዳንት መሰንበት ሸንቁጤን ጨምሮ ሌሎችም ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ተገኝተዋል። ዓለም አቀፍ የንግድ ትርኢቱ የገበያ ትስስር የሚፈጠርበት እና በዘርፉ የቴክኖሎጂ ሽግግር የሚከናወንበት መሆኑን የኢንዱስትሪ ሚኒስትሩ መላኩ አለበል በመክፈቻ ስነስርዓቱ ላይ ተናግረዋል፡፡ መንግስት በሀገር በቀል ኢኮኖሚ ማሻሻያው ልዩ ትኩረት ከሰጣቸው ዘርፎች አንዱ የማኑፋክቸሪንግ ኢንዱስትሪ ነው ብለዋል፡፡ ዛሬ የተከፈተው ዓለም አቀፍ የንግድ ትርኢትም ለኢትዮጵያ የማኑፋክቸሪንግ ኢንዱስትሪ የገበያ ትስስር እና የቴክኖሎጂ ሽግግር በመፍጠር ረገድ ሚናው የላቀ ነው ብለዋል። የአዲስ አበባ ንግድና ዘርፍ ማህበራት ምክር ቤት ፕሬዚዳንት መሰንበት ሸንቁጤ በበኩላቸው፤ የንግድ ትርኢቱ በማኑፋክቸሪንግ ለተሰማሩ አምራቾች የገበያ ትስስር ለመፍጠር እንደሚያግዝ ጠቅሰዋል፡፡ አያይዘውም እንደነዚህ አይነት የንግድ ትርኢቶች መዘጋጀታቸው የሀገር ገፅታን ለመገንባትና ኢኮኖሚውን ለማነቃቃት ትልቅ ፋይዳ አላቸው ነው ያሉት፡፡ በዓለም አቀፍ የንግድ ትርኢቱ ላይ ከ100 በላይ የሀገር ውስጥና የውጪ አምራች ኩባንያዎች፣ የቴክኖሎጂ አቅራቢዎች፣ አምራቾችና አስመጪዎች እንዲሁም ሌሎች ተቋማት ተሳትፊ ሆነዋል፡፡ ዓለም አቀፉ የንግድ ትርኢት ለአምስት ተከታታይ ቀናት ለጎብኚዎች በነፃ ክፍት ሆኖ እንደሚቆይ ተገልጿል፡፡

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *